የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሲቋቋም ዓላማው የአፍሪካ አገሮችን ነፃነት እውን ለማድረግ፣ አፍሪካውያን እንዲተባበሩ ለማስቻልና ከነፃነት ባሻገርም አፍሪካውያን የአፍሪካን ችግር ለመፍታት በጋራ እንዲንቀሳቀሱ ለማድረግ ነው፡፡የአፍሪካ አንድነት ድርጅትም ይባል፣ በአዲሱ ስሙ የአፍሪካ ኅብረት ብለንም እንጥራው ዓላማው ይኸው ነው፡፡በተጨባጭ የአፍሪካ ኅብረት ወቅታዊ እንቅስቃሴን ስናይና ስንገመግም ግን እኛ አፍሪካውያን የሚሰማን ምንድን ነው? ኩራት ወይስ ኀፍረት?በአይቮሪኮስት ‹‹ከምርጫው›› በኋላ በተከሠተው ሁኔታ ሕዝብ እያለቀ ነበር፡፡ ሥልጣን ልቀቅ አለቅም በሚል ጉዳይ በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ፈረንሳይ ወታደሮቿን አስገብታ የማረጋጋት እንቅስቃሴ አደርጋለሁ ትል ነበር፡፡ የአፍሪካ ኅብረትስ ምን አለ? ምን አደረገ? ያደረገው ነገር ካለስ የሚያኮራ ወይስ የሚያስነውር?በሶማሊያ በአሁኑ ጊዜ ሕዝብ በረሃብ እያለቀ ነው፡፡ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሠላሳ ሺሕ ሕፃናት ያለቁበትና የረገፉበት ሁኔታ ተስተውሏል፡፡ አንዲት እናት በአንድ ቀን አራት ሕፃን ልጆቿን ያጣችበትን ሁኔታ አፍሪካ አይታለች፡፡ አሁንም ያለው ስደት፣ አሁንም ያለው እልቂት ነው፡፡የአፍሪካ ኅብረት ምን እያለ ነው? ምንስ እያደረገ ነው? አፍሪካውያንና የአፍሪካ ኅብረት ዝም ብለው የቱርክ መሪዎች ግን ሞቃዲሾ ገብተው ሁኔታውን ሲያዩና ዕርዳታ ሲሰጡ እየተመለከትን ነው፡፡ አፍሪካኅብረትስ? አፍሪካውያንስ?የአፍሪካ ኅብረት በሶማሊያው ረሃብ ላይ እየወሰደ ስላለው ተጨባጭ ዕርምጃ እንኩራ ወይስ እንፈር?እኛ ኢትዮጵያውያንስ እንደ ኢትዮጵያዊነታችንና እንደአፍሪካዊነታችን ለተራበው የሶማሊያ ሕዝብ የሚገባንን እያደረግን ነውን? ረሃብና እልቂት ምን እንደሚመስል እኛ ኢትዮጵያውያን ከማንም በላይ እናውቀዋለን፡፡ በሶማሊያው እልቂት ምን ያህል ተሰምቶናል? ምን ያህልስ ደንግጠናል? ምን ያህል ያቅማችንን ያህል እንኳ ተንቀሳቅሰናል?ያለውን የፖለቲካና የጸጥታ ችግር ረስተነው አይደለም፡፡ ግን ምንም ነገር ላለመርዳት በቂና ሙሉ ምክንያት ሊሆን አይችልም፡፡ አፍሪካውያን ምን እያደረጉ ናቸው? ስንል በቅድሚያ ጐረቤትና አንድ ሕዝብ የሆነው ኢትዮጵያዊ ምን እያገዘ ነው ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ የራሳችን ችግርና ረሃብ ቢኖርብንም ሌላውን ትንሽም ብትሆን ላለመርዳት ሽፋን አይሆንልንም፡፡ሌላው በአፍሪካዊነታችን የአፍሪካ ኅብረትን የምንጠይቅበት አጀንዳ የሊቢያ ጉዳይ ነው፡፡ የሙዓመር ጋዳፊ ተቃዋሚዎች የሊቢያ ዋና ከተማ ትሪፖሊን እየተቆጣጠሩ ናቸው፡፡ ሕይወት እየጠፋ ነው፡፡ የተስፋ ብልጭታም ለሊቢያ ሕዝብ እየፈነጠቀ ነው፡፡ነገር ግን በሊቢያ ጉዳይም እየተንቀሳቀሱም እየተናገሩም ያሉት አሜሪካና አውሮፓ በተለይም የኔቶ አገሮች ናቸው፡፡ እነሱ ለምን ተንቀሳቀሱ፣ ለምን ተናገሩ አንልም፡፡ የአፍሪካ መሪዎች ግን በአፍሪካዊት አገር ጉዳይ ምን እየተናገሩና ምን እንቅስቃሴ እያደረጉ ነው? የሚያሳፍር ወይስ የሚያኮራ?የአፍሪካ ኅብረት በሊቢያ ጉዳይ ሊያፍር ይገባዋል፡፡ ሊያፍር የሚገባው ግን በሰሞኑ ይህን አለመናገሩ ወይም ያንን አለመተግበሩ ብቻ አይደለም፡፡ እንደ ሙዓመር ጋዳፊ ዓይነት መሪዎች በአፍሪካ መኖራቸውና የአፍሪካ ኅብረት አባልና አባል መሆናቸውም ሊያሳፍረን ይገባል፡፡ሊቢያ የዘይት ሀብት ቢኖራትም በቤተሰብ የምትተዳደር አገር፣ ተቋማት የሌላት አገር፣ ኋላ ቀር አገር ናት፡፡ አሁንም የዴሞክራሲና የሰብዓዊ መብት አጀንዳ የራቃትና መሪዋ ሕዝብን አይጥና ተምች እያለ የሚሰድብበት አገር ናት፡፡ሆኖም ግን የዘይት መዓት ገንዘብ ስለነበረ ጋዳፊ የአፍሪካ መሪዎችን በጉቦ የሚገዛበት ሁኔታ ነበር፡፡ ‹‹ንጉሥ ነገሥት ነኝ›› ሲሉ ‹‹አዎን ንጉሠ ነገሥት ናቸው›› የሚሉ የአፍሪካ መሪዎች አሉ፡፡ አፍሪካን ልምራ ሲሉ አዎን ጋዳፊ ይምሩን የሚሉ ነበሩ፡፡ የአፍሪካ ጽሕፈት ቤት ትሪፖሊ ይሁን ሲሉ አዎን ትሪፖሊ ይሁን የሚሉ ነበሩ፡፡ ባጭሩ ከጋዳፊ ምጽዋት የሚቀበሉ የአፍሪካ መሪዎች ነበሩ፡፡ ጥገኞች!እንደነሙዓመር ጋዳፊ ዓይነቱ መሪዎች ያቀፈና በነጋዳፊ ጉቦ የሚንቀሳቀሱ መሪዎች የያዘ የአፍሪካ ኅብረት የሚፈጥርብን ስሜት ኩራት ወይስ ኀፍረት?የአፍሪካ ኅብረት ራሱን መፈተሽና መገምገም አለበት፡፡ ለዴሞክራሲ፣ ለፍትሕ፣ ለሰብዓዊ መብት፣ ለፕሬስ ነፃነት፣ ለትክክለኛ ምርጫ፣ ለሰላምና መረጋጋት፣ ለብዙኀን ድምፅ የቆመ ኅብረት መሆን አለበት፡፡በአፍሪካ አገር ጉዳይ አሜሪካ፣ አውሮፓ፣ እስያና ላቲን አሜሪካ አያገባችሁም አንልም፡፡ ኦባማ፣ ካሜሩንና ሳርኮዚ ለምን ተናገራችሁ አንልም፡፡ የዓለም አካል ስለሆነች ስለአፍሪካዊት አገር መናገር ይገባቸዋልና፡፡ አጽንዖት ሰጥተን የምንናገረው፣ በአፍሪካ አገሮች ጉዳይ የአፍሪካ ኅብረት ግልጽና ቀልጣፋ፣ ጠንካራና መፍትሔ የሚያሳይ እንቅስቃሴ ማድረግ አለበት፤ አቋምም መውሰድ አለበት የሚለውን ነው፡፡ አፍሪካ ስትቸገር፣ ጠንካራና ግልጽ፣ ወቅታዊም አቋምና ተግባር በማይወስድ የአፍሪካ ኅብረት አፍሪካውያን የሚሰማን ስሜት ምንድን ነው?እፍረት !!!
EthioGreen

